Leave a comment

ክፍል ሦስት:- ለባለሀብቶች


ክፍል ሦስት

ለባለሀብቶች

ውድ የሀግሬ ወጣት ምሁራን ባለፉት ሁለት ትከታታይ ክፍሎች አንብባችሁ ለሰጣችሁኝ አስተያየትና ለጏደኞቻችሁ (share) ስላደረጋችሁ ዓላማየ መረጃ በመለዋወጥ ድርሻችን እንድንወጣ የሚል ስለሆነ ሦስተኛውን ክፍል እንድቀጥል ረድቶኛል:; አመሰግናለሁ::

በክፍል አንድ ለምሁራን ሰላምታ ባለሀብቶችንም ጨምሬ በያላችሁበት ሰላም እንድትሆኑ ተመኝቼ ክፍል ሁለት ላይ ትኩረትና ጫና ያድረግኩት ምሁራን ላይ ነበር አሁን ደግሞ ወደ ባለሀብቶች ጎራ ዘው ልበል:: ለምን እናንተንም ሰፊው የካፋ ወይም የድቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ማህበረስብ በናፍቆት ስለሚጠብቃችሁ::የሀገር ልማትና ብልፅግና የህብረትስቡ እድገትና ከድህነት መላቀቅ የምሁራንና የባለሀብት ጥምረት አንዱ ያለ ሌላው ቅንጅት የታሰበውን ውጤት በአጭር ጊዜ ውስጥ እውን ማድረ ስለማይታሰብ:::

ውድ ባለሀብቶች

እዚህ ላይ ባለሀብቱ ማነው? ማህበረስቡ መሆን ሲገባው ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆነና ጥቂት ቆሎ ይዘህ ወደ አሻሮ ተጠጋ እንዲሉ ጥቂት ሀብት ይዘው በልምላሜው ወደር የማይግኝለትን የካፋን ወይም የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ አካባቢን ጥቂት የማይባሉ ግለሰቦችና ቡድኖች በልማት ስም ወረው በጥቂት ዓመት ውስጥ ብዙዎች ሲከብሩ ህዝቡ ግን እንደ ግመል ሽንት በኑሮው የኃሊት በመሄድ ያለምንም እድገትና የኑሮ ለውጥ አመታትን አስቆጥሯል እያስቆጠረም ይገኛል:: ሆኖም ማህበርሰቡ ከዛሬ ነገ ባለሀብቶች ወደ አካባቢው ሲገቡ ሰንቀው የመጡትን የእድገት ራዕይ ይተግብራሉ ብሎ በተስፋ ሲጠብቅ ይባስ ብለው ሀብትና ንብረቱን ብቻ ሳይሆን ጉልበቱን ጭምር ያለአግባብ በመበዝበዝ ኢፍትሀዊ ተግባር ቢፈፅሙበትም በሰላምና በትዕግሥት እነሱ ለልጅ ልጅ የሚተርፍ ሀብት ሲያከማቹ እርሱና ልጆቹ ግን የበይ ተመልካች በመሆን በእድገት ጎዳና መጏዝ ስላልቻሉ “ኃላቀር” የሚል ታፔላ ተለጥፎባቸው ከሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች በታች መሆናቸው የአደባባይ ምሥጢር ሆኖ ቆይቷል ::የአካብቢው ሀብትና ንብረት ግን ያለምንም ቁጥጥር እየተጋዘ ወደ መሀል ሀገርና ሌሎች አካባቢዎችን በማልማት ላይ ይገኛል:: የጠላት ገንዘብ ይመስል ደን ይጨፈጨፋል (ይወድማል) በምትኩ ግን አይተከልም:: ፋብሪካ ሲያቋቁሙም አይታይም::

ሁለተኛ ሀገር በቀል ባለሀብቶችም አንድም ነገር አካባቢያቸው ላይ ሳይገነቡ የተለያዩ መሠረታዊ ግንባታዎች የጤና ተቋም ትምህርት ቤት ንፁህ የመጠጥ ውሀ ቀበሌን ከቀበሌ የሚያገናኝ መንገድ የሥራ እድል እንደየችሎታቸውና ለወጣቶችም አቅማቸው በፈቀደ ሠርተው እንዲለወጡ በመጠኑም ቢሆን የህዝቡን የኑሮ ደርጃ በሂደት መቀየር ሲገባቸው የአካባቢውን ሀብት ካጋበሱ በኃላ መሀል ሀገርና ሌሎች አካባቢዎች ላይ ፋብሪካዎች ሆስፒታሎች ሆቴሎች የትምህርት ተቋማት የህዝብ ማመላለሻ አውቶብሶችን የጭነት መኪናዎችን የመጠጥ ውሃ የለስላሳና የቢራ መጠጥ የእደ ጥበብ ወዘተ ፋብሪካዎችን ከአካባቢው በዘረፉት ጥሬ ሀብት ሲገንቡ ይታያሉ:: አስዛኝና አስፋሪ ድርጊት:: ከውጭ የሚመጡትም የማህብረስቡን መሠረታዊ ፍላጎት በማሟላት ፋንታ ሀብት ለማካበት ሲሽቀዳደሙና እቅድ አውጥተው የየራሳቸውን ሰዎች ጭምር ሳይቀር አሰማርተው ነዋሪውን ያለምንም ክፍያ ከቤት ንብረቱ አፈናቅለው አያት ቅድመ አያቶቹ ተንከባክበው ያቆዩትን የደን ሀብት አውድመው የአንበሳውን ድርሻ ሲውስዱ ህዝቡን የበይ ተመልካች አድገውታል::

ሶስተኛ ከነዚህ ባለሀብቶች ውጭ ህብረተሰቡ ማንነታቸው ባልታወቀ የንብረት ባለቤቶች ለምሳሌ በጊንቦ ወረዳ ውስጥ የውሽውሽ ሻይ ልማትን ብንወስድ አባቶቻችን ለዘመናት ተንከባክብውና ጠብቀው ያቆዩት ደን ተጨፍጭፎ ሻይ ከተተከለ በኅላ ለዘመናት ሲመዘበር ቆይቶ ዛሬ ላይ ባለቤት አልባ ቢመስልም በባለቤትነት በውል የታወቀ ግለሰብም ሆን ቡድን ይፋ ወጥቶ ሲነገር ባይሰማም ሸህ አላሙዲን መለስ ዜናዊ አዜብ መስፍንና አሁን ላይ ደግሞ ጌታቸው አሰፋ በባለቤትነት ሲታሙ ይሰማል:: ጥያቄውን ለጊንቦ ወረዳ አስተዳዳሪዎች መልስ እንዲሰጡ ህዝቡ ይጠይቃል (የውሽውሽ ሻይ ልማት የማን ነው? የህዝቡ? የካፋ አስተዳደር ባለሥልጣናት? የፌደራል መንግሥት? የዴህዴን? ወይስ የቻይና? እኮ የማን???:: የህዝቡን ጉልበት ላለፉት 27 አመታት በሠራተኛ ስም በባርነት ሲገዙት የልማቱ ባለቤት ማንነት አለመታወቁ ተጠያቂ መጥፋቱ ያልተፈታ እንቆቅልሽ::

ለዘመናት የተመዝበረው የአካባቢው ማህበረሰብ ሀብት ገንዘቡ የት ገባ? ጥሬው የሻይ ቅጠል ወደ ፍጆታ የሚለውጠውና አሽጎ ለገበያ የሚያቀርብው ፋብሪካ የት ነው የተቋቋመው? ባለቤቱስ ማን ነው?? የምታውቁ አትጠፉምና የምዝቡራው አካል ካልሆናችሁ:: ይገርማል:: መንግሥት አልባ የሆነ በቁሙ ከነነፍሱ የተሸጠ ህዝብ የሚኖርበት እካባቢ:: እናውቃለን ብንናገር እናልቃልን:: ለዚህም ነው ምዝበራው ያንገሸገሸው የካፋ ህዝብ የክልል ጥያቄ አንስቶ ሰሚ ባያገኝም እንኳን (አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ) እየሆነበት ለዘመናት በሰላማዊ መንገድ ድምፁን በማሰማት ላይ የሚገኘው:: ጥያቄውን መመለስ አግባብነት እንዳለበት እየታወቀ የባለሀብቶችና የአንዳንድ የግል ጥቅም አሳዳጅ ባለሥልጣናት ተፅእኖ መፍትሄ ከመፈለግ ይልቅ ጉዳዩን ውስብስብ ሲያደርገው ይስተዋላል::

ታዲያ እውነታው ይሄ ከሆነ ባለሀብቶችንና የህዝብ አደራ የተጣለባችችሁ ባለሥልጣናት ያለፈው አለፈ:: ላለፈ ክረምት ቤት አይሰራም:: የአከባቢው ማህበረሰብ በእድገት ኃላ ቀርነት ወደዳችሁም ጠልችሁም ከናንተ ራስ እይወርድም:: ታሪክም ሥራችሁን መዝግቦ ለትውልድና ለልጅ ልጆችችሁ ማስተላለፍ ግድ ነው:: ነገር ግን ይህን የበደላችሁትን የዋህ ህዝብ የምትክሱበትና አሳፋሪውን ታሪክ ከስህተታችሁ ራሳችሁ ተምራችሁ አዲስና እኩሪ ታሪክ የምታስመዘግቡበት የተሐድሶ ወቅት ላይ ስለምትገኙ ይህን አጋጣሚ ተጠቅማችሁ ሁኔታዎችን በማገናዘብ ከህዝብ ጎን በመቆም:

1ኛ/ የክልል ጥያቄው ህገ መንግሥቱን ተከትሎ በአግባቡ በአስቸኳይ እንዲመለስ ጫና ማድረግ (ተሰሚነት ስላላችሁ የህዝቡን ድምፅ በሰልማዊ መንገድ አስተጋብት)
2ኛ/ ለዘመናት ሀብትና ጉልበቱን የመዘበራችሁትን ማህበረሰብ አስፈላጊውን መሠረተ ልማት መዋቅር ተባብራችሁ በመዘርጋት ሌሎች መሰሎቹ የደረሱበት የእድገት ደረጃ ላይ እንዲደርስ ማድረግ
3ኛ/ ሀብትና ንብረቱ ላይ የመወሰን (እናንተም ህዝቡም) ተጠቃሚ የሚሆንቡትን መንገድ ማመቻቸት

4ኛ/ የለውጡ አጋር በመሆን ወደፊት በምገነባው ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆን ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝብ ህብረት ጎን በመቆም (በመተባበር) አስፈላጊውን አስተዋፅኦ በማድርግ የፋይናንስ ድጋፍና የማስተማር የማንቃትና ማደራጀት ወዘተ ድጋፍ ይጠበቅባችኃል

አንዳንዴ ከቀለም ትምህርትና ከሀብት ወጣ ብሎ እድማስን አስፍቶ አካባቢን አጥንቶ ለህብረተሰቡ የሚበጅ መልካም ነገር ማድረግ ከምሁራንና ከባለሀብት ይጠበቅባችኃል::እንደምታውቁት አካባቢው አመቱን ሙሉ በልምላሜ የታደለና የሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ለሚመጡ የሀገር ጎብኝዎች ቀልብ የሚስብ የድን ሀብትና የተለያዩ የቅመማ ቅመም የአእዋፍ የእንስሳት ዝርያዎች ማእድናት ማር ወንዞችና ፏፏቴዎች ፍልውሀዎች ወዘተ እያለው ነገር እሱ በሀብትና ንብረቱ ተጠቃሚ ሳይሆን ዘመናዊ የገባር ሥርዓት ተጭኖበት ላለፉት ምዕተ አመታት ሲበዘበዝ ሲጨቆን ኖሯል:: አሁን ግን ይብቃኝ እያለ ስለሆነ ልንተባበረው ግድ ይላል:: ይህ ካልሆነ ግን ከዝምተኛና ከረጋ ውሀ ተጠንቀቅ እንዲሉ የካፋን ህዝብ ጀግነትና ቆራጥነት ለማወቅ የተለያዩ የታሪክ ምሁራን የዘገቡትን ታሪኩን አለመረዳት ይሆናል:: ልብ ያለው ልብ ይበል ይሏል::

አንድነት ህይል ነው ትዕግሥት የአስተዋይነት ምልክት እንጂ የፍርሐት አይደለም:: ሰላምና ፍቅር ካለን ከራስችን አልፈን ለሌሎች እንተርፋሉን:::ኢትዮጵያ ሀገራችንንም የበለጠ ተጠቃሚ እናድርጋለን::

በተመሳሳይ እርእስ እስክንገናኝ ቸር ይግጠመን::

ፋንታዬ መኮ
ነሐሴ 23 ቀን 2011 ዓም
29 August 2019
ካፋ ሚድያ kaffamedia

Leave a comment