Leave a comment

ኑ የጋራ ቤታችንን በደቦ አብረን እንስራ!!


ኑ የጋራ ቤታችንን በደቦ አብረን እንስራ!!!

 

ሰሞኑን ውድና ብርቅየ ከሆኑ የደምኢሕህ ኣባላት መካከል ኣንዱ የሆነው ኣቶ ኣማኑኢል ካርሎ በተደጋጋሚ Kaffamedia ድህረ ገፅ ላይ ጠቃሚ ሀሳቦችና ኣስተያየት ዘርዘር ባለ መልኩ ሲያቀርብ ተመልክቻለሁ::

 

ሌሎችም ኣቶ ብርሁኑ ወ/ስንበት ኣቶ ተስፋየ ወ/ሚካኢል ኣቶ ጎዲ ባይከዳና ኣቶ ያሮን ቆጭቶ በተለያየ ወቅት ገንቢ ኣነቃቂና ኣስተማሪ የሆኑ ጽሑፎችን በማሰራጨት መረጃዎችን በማካፈል ባጠቃላይ የህዝቡን ብሶት በማሰማት ታግለው በማታገል ላይ ይገኛሉ::

 

በመቀጠል ተጨባጭ የሆነ ኣስተዋፅዖ በማድረግ ያለ የሌለ ጊዜኣቸውን ገንዘባቸውን ጉልበታቸውና እውቀታቸውን በነፃ በመለገስ ደከመን ሰለቸን ሳይሉ ሰንቀው ለተነሱበት ዓላማና ራዕይ ከሩቅ ሆነው የወገናቸውን የልብ ትርታ በማዳመጥ ብሶቱ ጭቆናውና በድህነት ኣሮንቋ ውስጥ ተዘፍቆ የፍትህ ያለ እያለ ሲጮህ ሰሚና ተቆርቋሪ ሆነው የትግሉ ኣጋር በመሆን ለሚመለከተው ክፍል ጥያቄዎቻቸው ቢያቀርቡም ተቀባይነት ባለማግኘታቸውና ይባስ ብሎ የሥርኣቱ ተገዥ በሆኑ ካድሬዎችና ለሆዳቸው ባደሩ ባንዳዎች በደረሰባቸው ወከባ ከሚወዱትና ከሚቆረቆሩለት ህዝብ ተለይተው በውጭ ሀገር ተሰደው መታገልን እንደኣማራጭ ወስደው እነሆ በኣይነቱ የመጀሙሪያ የሆነ ድርጅት “የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝብ ህብረት (ደምኢሕህ)” መሥርተው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ::

 

ውድ ወገኖቼ

እኔ በግሌ ለነዚህ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች የማይሞከረውን የጭቆና ቀንበር ከወገናቸው ጫንቃ ላይ ለኣንዴና ለመጨረሻ ከሥሩ መንግለው ለመጣል ፈር ቀዳጅ የሆኑ ውድና ብርቅየ ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝብ ኣብራክ የተገኙ የቁርጥ ቀን ልጆች ላዱረጉትና በማድረግ ላይ ላሉት ኣስተዋፅዖ ከፍ ያለ ምሥጋና ሳቀርብላቸው ከታላቅ ኣክብሮት ጋር ሲሆን ብዙዎቻችሁ ሀሳቤን ትጋሩኛላችሁ የሚል እምነት ኣለኝ::

 

በነገራችን ላይ እነዚህ ግለሰቦች ይህን ድርጅት ሲመሰርቱ ኣንዳንዶቻችሁ እንደምታስቡን የግል ጥቅምና ዝና ወይም ሹመትና ሥልጣን ናፋቂ ሆነው ሳይሆን ወገናቸው ላይ እየተፈፀመ ያለው ግፍና በደል ጭቆናና እንግልት በገዛ ምድሩ ላይ ሰርቶ እንዳይኖር ኢኮኖሚያዊና ሳይኮሎጂካዊ ተፅእኖ ታውጆበት ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት መሰል እህትና ወንድሞቹ በእኩል ኣይን ሳይታይ በሀገሩ ላይ ሰርቶ የመኖር የመማር የመበልፀግና የማደግ መብቱ ተገፎ እንደ ግመል ሽንት ወደ ኃላ እየተራመደ ከማጡ ወደ ድጡ እየወረደ መቶ ኣመት ሆንው:: ዛሬም የለውጡን ችቦ ለማቀጣጠል ጥረት ቢያደርግም ከመንግሥት በኩል ለሌሎች እየተደረገ ያለው ድጋፍና ማበረታታት ሲደረግለት ኣይታይም (ምክንያቱ ግልፅ ባይሆንም):: ዛሬም ከቀየው እየተፈናቀለ መሬቱ ለሌሎች ይታደላል:: ኣያት ቅድመ ኣያቶቹ ከወራሪወቹ ጋር ተፋልመው ኣልበገር ብለው መስዋዕት የከፈሉበት ዳር ድንበሩ ተደፍሮ ከማንኛውም መሠረተ ልማት ተጠቃሚ እንዳይሆን የትምህርትና የእውቀት እድል ተነፍጎት ወደ ፊት እንዳይሄድ መብቱን እንዳያስከብርና ጥያቄ እንዳይጠይቅ ኣፉን ተሸብቦ ገዚው መደብ የራሱ ልጆች መልሰው እንዲወጉት በጥቅማ ጥቅሞች በመደለል የራሳቸውን ህልውና ሸጠው ህዝቡ በማንነቱ እንዳይተማመን የበይ ተመልካች ሆኖ ተነሳ ሲሉት የሚነሳ ተቀመጥ ሲሉት የሚቀመጥ ተንቀሳቃሽ ፍጡር /robot እንዲሆንላቸው ተደርጓል:: ምሁሩም እዳር መቆምን የመረጠ ይመስላል::

 

ይህ ነው ደምኢሕህ እንዲያቋቁሙ የገፋፋቸው እንጂ እነሱማ ዴሞክራሲ የሰፈነበት እንኳን የሰው የእንስሳት መብት የተከበረበት ከየትኛውም ዓለም ይምጣ በህጋዊ መንገድ እስከ ገባ ድረስ የዘር የፆታ የቀለምና የሀይማኖት ልዩነት ሳይደረግበት በእውቀቱና በኣቅሙ በየትኛውም ቦታ በነፃነት ተዘዋዉሮ ሠርቶ የሚኖርበት ዓለም ውስጥ ናችው ምንም የጎደለባቸው ነገር የለም:: የሚታገሉትም ይህን መሰል ሥርዓት ወደ ህዝባቸው ለማስረፅ ነውና ከጎናቸው በመቆም ላልሰማ እናሰማ ላላወቀ እናሳውቅ እላለሁ::

 

በዚህ ኣጋጣሚ ማንኛውም የድርጅቱን ኣላማ የሚደግፍ የለውጥ ኣራማጅም ሆነ ኢሃድግን ሲደግፉ የኖሩ ወገኖቻችን ድርጅቱ የህዝባችን ድምፅ ስለሆነ ምንም እንኳን ላለፉት 27 ዓመታት በማወቅም ሆነ ባለማወቅ በፍላጎትም ሆኑ ተገዳችሁ ከህዝብ ጎን ሳይሆን ከተቃራኒ ጎራ የነበራችሁ ዘመኑ የፍቅርና የይቅርታ ስለሆነ ፊታችሁን ወደ ወገኖቻችሁ ጊዜው ሳይመሽ መልሱና የበደላችሁትን ህዝብ ካሱ “ኑ የጋራ ቤታችንን በደቦ ኣብረን እንስራ”:: እንረዳዳ ኣንድ ሆነን ኣብረን እንቁም መለያየት ኣይበጀንምና በኣንድ እጅ የሚያጨበጭብ ሰሚ የለውም እንወያይ እንመካከር ልዩነትን እናጥብብ ከሌሎች እንማር “ትግራይ ኦነግን ማስተናገድ? የኦነግም መስተናገድ መቻቻልን ያሳየናል እያለ ጅርጅታችሁ በሩን ክፍት ኣድርጎ ይጠብቃችኃል “ኣይጥና ድመት ተስማምተው በጋራ ሲገባበዙ እኛ ኣንድ ህዝቦች ስንሆን መናቆር ምን ኣስፈለገ? በተለይ ምሁራኖች እባካችሁ ወደ ኣንድነት ኑ ጎራ ለይታችሁ የጎሪጥ መተያየት ከናንተ ኣይጠበቅምና::

 

ድርጅቱን የጀርባ ኣጥንት በመሆን በሀሳብ በሞራል በገንዘብ በጉልበትና እንዲሁም ከካፋ ሚዲያ በተጨማሪ መረጃ በማስተላለፍ እየረዱ ያሉ ሁለት ብርቅየ ወጣቶች መካከል::

 

1ኛ/ ህዝቡን ለረጅም ኣመታት በሶሻል ሚድያና በራሱ የተለያየ ድህረ ገፅ ከፍቶ በማንቃትና በማደራጀት ከፍተኛ ሚና በመጫወት ከፍተኛ ኣስተዋፅኦ በማድረግ ላይ የሚገኘውን ወጣት ቁምላቸው ኣምቦ

 

2ኛ/ የተጠየቀውን ብቻ ሳይሆን ያልተጠየቀውን ጭምር ድጋፍ በመስጠት በማንኛውም ጊዜ ከድርጅቱ ጎን የቆመ ዋልታና ምሱሶ የሆነውንና ኣደባባይ ቆሞ በቪድዮ ለቴፒ ህዝብ ጉዳይ ድምፅ ያሰማ ብቸኛው ኣክቲቪስት ወንድወሰን ግዛው

 

እነኚህ ሁለት ወጣቶች በግሌ ኣመሰግናቸዋለሁ ኣከብራቸዋለሁ:: ሊመሰገኑና ሊበረታቱ ይገባል እላለሁ::

 

በመጨረሻ ሀሳቤን ለማጠቃለል በሶሻል ሚዲያው ላይ ኣንዳንድ ወጣቶች ኣላስፈላጊ ቋንቋዎችን በእውቀትም ሆነ ያለ እውቀት ሲጠቁሙ ይታያሉ:: ይህ በጣም ኣስፀያፊና ኣሳፋሪ ስለሆነ እባካችሁ ሃሳብን በሀሳብ ሞግቱ እንጂ ፀያፍ ቃላት ስትለዋወጡ ያስገምታችኃልና ታቀቡ:: ተጠቃሚዎቹ ትንሽም ቢሆን ፊደል የቆጠራችሁ ናችሁና::

 

ዛሬ ኣንድ መፅሐፍ ላይ ያነበብኩትን ላካፍላችሁና ሁሳቤን ልቋጭ

“He who does not have the courage to speak up for his rights cannot earn the respect of others” Rene G. Torres

 

የደቡብ ምዕራብ ህዝብ ያልተሰማው ቀደም ብሎ እንደ ቄሮና ፋኖ ድምፁን በድፍረት ኣደባባይ ወጥቶ ባለማሰማቱ ይመስላል:: ዝምተኛን ልጅ እናቱ ትረሳዋለች ይባል የለ!!!!

 

ዝም ኣንበል ለመብታችን በጋራ እንታገል!!!

ቸር ይግጠሙን!!!! Share በማድረግ ተባበሩ::

ከፋንታዬ መኮ

ካፋ ሚዲያ kaffamedia

Leave a comment